Tuesday, May 26, 2015

ስትመርጥ የኖረች ሴት

ስትመርጥ የኖረች ሴት

(ውብሸት ታደለ)

ትረፍ ሲለኝ እንደ2002ቱ ምርጫ ሁሉ በዚህ መሳቂያ ምርጫም እጄን አላነካካሁም፡፡ ኢህአዴግ በቡጢ እንጅ በምርጫ እንደማይወድቅ ባውቅም የሰላማዊ ትግሉን የመጨረሻ ሙከራ ለመደገፍ አስቤ ካርድ ልወስድ ነበር፡፡ ሚካኤል በምህረቱ ዳሰሰኝና የውርደት ካርዱን ሳልቀበል ቀረሁ፡፡ ምናልባት ቀን ሲያልፍ ለልጄ በኩራት እነግረዋለሁ፤ “እኔ አባትህ ካርድ አልወሰድኩም ነበር” እያልኩ አወራዋለሁ፡፡

ያላደላቸው ወገኖቼ ካርዱን እንደዳረጎት እጅ ነስተው በመቀበላቸው በምርጫ ጣቢያው ተገኝተው ‘ይሆነኛል’ ያሉትን ጨጓራ በሽታን መርጠዋል፡፡ ከምርጫ ጣቢያው መልስም ወደ ጤና ጣቢያ እንዳዘገሙ ዘገባዎች ያመለክታሉ J

የመኢአድ ሊቀ-መንበር በክርክሩ ወቅት የተናገሩት ነገር አሁን ግልፅ እንደሆነላቸው መራጮቹ ለራሳቸው ተናግረዋል፡፡ ሊቀ-መንበሩ በክርክሩ ጊዜ ‘ህዝቡ በደም ግፊት ምናምን የሚጠቃው በሚደርስበት በደል እየተበሳጨ ነው’ ሲሉ ተናግረው ነበር፡፡ ዶ/ር ቴወድሮስ ይህን ነገር በጤና ፖሊሲው ውስጥ እንዲካተትና በምርጫ ቦርድና በኢቢሲ ምክንያት የሚከሰቱ በሽታዎችን እንዲቀንሱ አደራ እንላለን፡፡

ከዚሁ ጋር በተያያዘ ኢህአዴግ ለስኪዞፍሬንያ (የዕብደት በሽታ) መንስኤ ሆኖ ስለተገኘ አሳብዶ ሳይጨርሰን በፊት የአዕምሮ ጤናን በተመለከተ በኢህአዴግ ላይ ትኩረት ተደርጎ እንዲሰራ ለዶ/ር ቴወድሮስ አደራ እላለሁ፡፡ መቼም ዶ/ሩ “የውጭ ጉዳይ አይለምደኝም” ብለው ወደጤናው ይመለሳሉ ብዬ ነው አደራውን ለእርሳቸው መስጠቴ፡፡ እንደሌሎቹ ነባር ጓዶቻቸው ‘በእልህ መንቦራጨቄን እቀጥላለሁ’ ካሉም መንገዱን ጨርቅ ያድርግላቸው፡፡ ያውም የአልመዳ ጨርቅ! J በነገራችን ላይ ኮሮጆውን ያመረተው አልመዳ ነው የተባለው እውነት ነው? እንዲያውም ኢህአዴግ ምርጫውን ያዘጋጀው ከምርጫው ሳይሆን ከኮረጆው የሚያገኘውን ትርፍ አስቦ ነው ይባላል J

ድሮ ድሮ ኮረጆ ሲባል ቶሎ ወደአዕምሯችን የሚመጣው የቆሎ ተማሪ ነበር፡፡ ኮረጆ የምፅዋት መቀበያ ዕቃ ነበር፡፡ አሁን ግን ዕድሜ ለወያኔ ኮረጆ ሲባል ትዝ የሚለን ኢህአዴግ ነው፡፡ አሁን ኮረጆ የልመና ሳይሆን የዝርፊያ ዕቃ ነው፡፡ ከተመፅዋቾች ይልቅ ሌቦችን ያገለግላል፡፡

ድሮ ድሮ ካርድ ሲባል ትዝ የሚለን ጤና ጣቢያ ነበር፡፡ ካርድ የፈውስ ትኬት ነበር፡፡ አሁን ግን ዕድሜ ለገዢዎቻችን ካርድ ሲባል ትዝ የሚለን ምርጫ ጣቢያ  ነው፡፡ አሁን ካርድ የህመም ትኬት ነው፡፡ በውርደት ስሜት ምክንያት ለሚመጣ የጨጓራና የዕብደት በሽታ ያጋልጣል፡፡ ይህን በሽታ ለሃኪም ከተናገራችሁ ደግሞ ከጤና ጣቢያ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ትዛወራላችሁ፡፡

በነገራችን ላይ አንድ ለአምስት አደረጃጀት በህመምተኞች ላይ አልተሞከረም እንዴ? በመራጮች ላይ ተሞክሮ እኮ አመርቂ ውጤት አስገኝቷል፡፡ አንድ ሰው የአራት ሰው ድምፅ ይሰጣል፣ አንድ ሰው አራት ሰው ከምርጫ ጣቢያ ያባርራል፣ ወዘተ፡፡ እናንተዬ! እኔ የምፈራው ግን ወሲብ በአንድ ለአምስት ይሁን እንዳይሉን ነው ሃሃሃ አንድ ካድሬ ለአራት ሴቶች J

ጥርሴ ይርገፍ! አሁን ይሄ ከምርጫው በላይ የሚያስቅ ነገር ሆኖ ነው?!

…….

አንዲት ወዳጄ (ትደግዬ) በዚህ ወቅት አንድ የበዕውቀቱን ግጥም አስታውሳኛለች… “ስትፈጭ የኖረች ሴት”፡፡ በእርግጥም ስትፈጭ ኖራ በፈጨችበት ድንጋይ መቃብሯ የሚከደን ያች የገጠር እህታችን ስለዚህ ጉድ ምን ታውቃለች?!

እሷ የምታውቀው መፍጨት ነው፡፡ ገዢዎቿ ዱቄቷንም ድምጧንም ከከረጢቷ ይዘርፋሉ፡፡ ዱቄቷም ድምጧም የት እንደገቡ አይታወቅም፡፡ በሲሲፈስ ብርታት ሁሌም ዱቄት ትፈጫለች፤ ዱቄቱ ግን ቋቷን አይሞላም፡፡ በሲሲፈስ ብርታት ሁሌም ድምጧን ትሰጣለች፤ ድምጧ ግን ለገደል ማሚቶ እንኳን አይበቃም፡፡ … ስትመርጥ የኖረች ሴት!

“አታውቅም…
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ማን እንደሚባሉ
ሹማምንት በሷ ስም ምን እንደሚሰሩ
አነሳሁት እንጅ እኔም ለነገሩ
በፖለቲክ ጥበብ ራስን ማራቀቅ
ምን ይጠቅማትና ጓያዋን ለማድቀቅ”

(ካልረሳሁት እንዲህ እያለ ነው ግጥሙ የሚቀጥለው)

(በእንዲህ መልኩ ነው ኢህአዴግም የሚቀጥለው)

ሙሉውን ግጥም በማንበብ ሙሉውን የምርጫ ሂደት ይከታተሉ J … “ከቋት ስስት እንጅ ዱቄት አይታፈስ”!!

ግን በዘንድሮው ምርጫ ማን ያሸንፍ ይሆን?  J J 

ተስቶት ኢህአዴግ ካሸነፈ ግን ፕ/ር መርጋ ጠቅላይ ሚኒስትር ይሆናሉ… እየተባለ ነው ሃሃሃ
…….



No comments:

Post a Comment