Tuesday, January 31, 2012

የኛ ጉዳይ


1. ሰሞኑን በተሳተፍኩበት አንድ ውይይት ላይ ለአደንዛዥ ዕፅ ሱስ መስፋፋት ምክንያቱ የትውልዱ የሞራል ዝቅጠት ነው የሚል ሃሳብ ካንድ ምሁር ቀርቦ አሳፋሪ ክርክር አድርገንበታል፡፡ ሱሰኝነትን ከሞራል ዝቅጠት ጋር የሚያይዝ “ምሁር” በዚህ ዘመን ማግኘት ከባድ ነበር፤ አገሪቱ ብርቅዬ እንስሳትን ጨምሮ ብዙ ብርቅዬ ነገሮች ስላሉባት ግን ብዙ አልተደነኩም፡፡
2. ከወራት በፊት ራሱን ባጠፋው የኔሰው ገብሬ አሟሟት ዙሪያ በተለያዩ ፀሃፍትና ምሁራን የቀረቡ ሃሳቦችም ከፖለቲካ ብሶት በስተቀር የሚጨበጥ የሞራል ትንታኔ ማቅረብ አልቻሉም፡፡ ብዙዎች በየኔሰው ጤና ዙሪያ ከጥርጣሬ እንዳልፀዱ በቅርብ የገጠመኝ ሰው እማኜ ነው፡፡
3. ቀደም ብሎ በጁፒተር ሆቴል ተካሄዶ የነበረውን የHomosexuals ስብሰባን በተመለከተ የተለያዩ ፀሃፊዎች የፃፉት ጫጫታን እንዲሁም በጉዳዩ ላይ ክርክር ለማድረግ አለመፍቀዳቸውን ታዝቤአለሁ፡፡
4. ሰሞኑን ደግሞ Tsegaye Hailesilassie በፌስቡክ ሰሌዳው ላይ በAtheists ላይ የሰነዘረውን ጉንተላ ተከትሎ የተደረጉት ክርክሮች በJudo-christian እይታ ተፅዕኖ ስር የወደቁና የፅንሰ-ሃሳብ ዕጥረት የሚታይባቸው ሆነው አግኝቻቼዋለሁ፡፡
ይህ ሲጠራቀም ኢትዮጵያውያን ምሁራንና ፀሃፍት ከፖለቲካ ባሻገር ትርጉም የሚሰጥ ሃሳብ ማመንጨት አይችሉም ወይ የሚል ብሶት ተናነቀኝ፡፡ ብሶቴን ተጋሩኝ!

Friday, January 27, 2012

አገሬ!


"…የግጦሽ ሳር ሲለመልም፤ ሲሰማሩ ሰደድ ሜዳ
አዝመራው ጣል ከንበል ሲል፤ ከብቱ ለሆራ ሲነዳ
ፈረስ ግልቢያ ስሸመጥጥ፤ ከወፎች ዜማ ስቀዳ
ልቤ በንፋስ ተንሳፎ፤ በዋሽንት ዋይታ ሲከዳ…
ያችን ነው ኢትዮጵያ የምላት
እመብርሃን ረሳሻት?"
__________________________________[ሎሬት ጸ.ገ.መ]
በአቡነ ጴጥሮስ ሰቆቃ ውስጥ ልጅነት ያተመው የትዝታ ዱካ ነፍስ ዘርቶ አቡኑን ሲያንሰቀስቃቸው እንሰማለን፡፡ አገር ማለት ምንድነው ለሚሉ የሎሬቱን ፍልስፍና በአቡኑ ትናጋ እንዲሰሙ እመክራለሁ፡፡ "ያችን ነው ኢትዮጵያ እምላት"፡፡ ሰው በልጅነቱ ይዞት ከሚወለደው ቡጫቂ ስጋ ይልቅ በህይወት ዘመኑ በምግብና በስራ የሚገነባው ይበልጣል፡፡ ይህ ራሳችን የገነባነውን ስጋ ራሳችን በቀላሉ ቆርጠን መጣል አንችልም፤ ህመሙ ስፍር የለሽ ነው፡፡ መንፈስም ከስጋ የተለዬ አይደለም፡፡ በሕይወት ውጣውረድ የተገነባ የአገር ፍቅርን ቆርጦ መጣል አይቻልም፡፡ ልምዱን ሌላ ቦታ ሌላ አገር ማዳበር ሊቻል ይችል ነበር፡፡ ግን አልሆነም፡፡ የልጅነት ስጋና መንፈስ የተገነቡት በዚች አገር ዳረንጎት ነው፡፡ ከአዳም ዕድሜ በኋላ የምናልፍበት የህይወት ቁልቁለት ሁሉ ለማንነት ብዙም እርባና የለውም፡፡ ሲግመንድ ፍሮይድ እንዳለው ልጅነት የማንነታችን መሰረት ነው፤ ካለዚህ መሰረት ማንነት ይሉት ጎጆ አይታሰብም፡፡
"…ያችን የልጅነት እናት
አዛኝቱ እንዴት ብለሽ ጥርሶችሽን ትነክሽባት?"

Thursday, January 26, 2012

አልታሰረችም


እውነት በፃፈ እጇ ላይ
ገመድ ተበተቡ አሉ
የሚፃፈው በአዕምሮ እንጅ
ከቶ በጣት እንዳልሆነ
የዘነጉ ቂሎች ሁሉ፡፡
  --------ለርዕዮት አለሙ እና መሰሎቿ