Wednesday, October 7, 2015

ዋዛና ቁምነገር



ዋዛና ቁምነገር

(ውብሸት ታደለ)

ማሳሰቢያ፡

ማህበረሰብን ወይም ባህልን  ተችቶ መፃፍ ዕዳ ነው፡፡
እንደእውነቱ ከሆነ ቢያንስ ግማሹ የማህበረሰብ ታሪክና ሁለንተና እከክ አለበት፡፡ ስለዚህ አልፎ አልፎ በምፅፋት ትችት ቀርቶ ዕድሜ ልኬንም ህዝቤንና ባህሉን ስተች ብኖር እከኩ አይራገፍም፡፡ ለውጥና መሻሻል የሚመጣውም በትችትና ትችትን ተከትሎ በሚመጣ ክርክር ነው፡፡ ስለዚህ የፅሁፍን ፍሬ ነገር አንብቦ ከመሟገት ይልቅ ማለቃቀስም ሆነ መሳደብ ወይም አዕምሮዬን ለማንበብ መሞከር ያስቀስፋል ፡) ያስቀስፋል ብያለሁና ማንም ይችን ሙከራ የሚሞክራት ሰው እንደማይኖር እርግጠኛ ነኝ፡፡ ፡)

***
ሃበሻ ዋዘኛ ነው፡፡

“ዋዛ” የምትለዋን ቃል ስፈልግ ያገኘኋት ከአቤ ቶክቻው “ዋዛና ቁም ነገር” የተሰኘ የኢሳት ፕሮግራም ላይ ነው፡፡ ዋዛ ምንድነው? እኔ ይህችን ቃል በዋዛ አላያትም፡፡ ዋዛ የቸልተኝነትና የዘፈቀደ ድምፅ ናት፡፡ ዋዘኛ ሰው ህይወትን አቅልሎ ይመለከታል፤ ቁምነገር አጠገቡ አይደርስም፡፡ አቤ ቶክቻው የማይታረቁትን ነገሮች አንድ ላይ አመጣቸው…ዋዛና ቁምነገር፡፡ ዋዛ እና ቁምነገር አብረው አይሄዱም፡፡ ዋዛ የሰነፎች፣ የደካሞች፣ የመሃይማን መደበቂያ ነው፡፡

እና የማይገባኝ ነገር…

ፖለቲካን ያክል ቁምነገር ለማውራት ዋዛ ለምን ያስፈልጋል የሚል ነው፡፡ ፖለቲካ ከነስሜቱና ወኔው የሚገለፅ ካልሆነ በፈገግታና በዘፈቀደ የምናወራበት ጉዳይ አይደለም፡፡ ታዲያ ዋዘኞች ለምን በዙ? ዋዛ ዕውቀት አይጠይቅም፡፡ አንድ የሰፈር ጎረምሳ ሃያ አራት ሰዓት በባለስልጣኖቻችን ላይ ሙድ ሊይዝ ይችላል፡፡ ሊስቅና ሊያስቅ ይችላል፡፡ ፖለቲከኞቻችንን የሚፈትን፣ የፖለቲካችንን አቅጣጫ የሚወስን ቁምነገረኛ ሃሳብ ግን ማቅረብ አይችልም፡፡ ይህ ዕውቀትና ሃሳቢነትን ይጠይቃል፡፡

ከዋዛ ጋር ብዙ ጊዜ አብሮ የሚመጣው ቀልድ ነው፡፡ ቀልድ ጭቆናን የመለማመጃ አንዱ ዘዴ ነው፡፡ በጭቆናው ላይ የሚቀልድ ህዝብ ከጭቆናው ሊላቀቅ አይችልም፤ በፍፁም፡፡ በዋዛ ላይ የተመሰረተ ፖለቲካ ጭቆናን አቅልለን እንድናዬው ከማድረግ ያለፈ ዋጋ የለውም፡፡ ከጭቆና ለመውጣት ቁጡና አልቃሻ ብዕሮች ያስፈልጉናል፡፡ ያ ትውልድ ወደአገራችን ካስገባቸው እንግዳ ባህሎችና አስተሳሰቦች መካከል ቁምነገረኝነት አንዱ ነበር፡፡ ታዲያ የሚገርመው… የትውልዱ እርግማኖች አብረውን አሉ፤ በረከቶቹ ግን ወደመጡበት ተመልሰዋል፡፡ ነፃነት፣ እኩልነት፣ ቁምነገረኝነት እንደአመጣጣቸው ተመልሰው ሄደዋል፡፡ ሴራ፣ ፍረጃ፣ ጎሰኝነት አጎዛ ተነጥፎላቸው ተቀምጠዋል፡፡

ዋዘኝነት እንደገና አገሪቱን ተረክቧል፡፡ እንደተመስገን ደሳለኝ የገዢዎቻችንን ልብ የሚያርበተብቱና የህዝብን ህሊና የሚያነቁ ሰዎች ያስፈልጉናል፡፡

በዚህ ዋዘኛ ህዝብ መሃል እንደዚህ ዓይነት ሰዎች ማግኘት ግን እጅግ ከባድ ነው፡፡ ቢገኙም እንኳን ቁምነገረኛ ሆነው የመቀጠል አዝማሚያቸው ደካማ ነው፡፡ የማህበረሰቡም ሆነ የፖለቲካው ስርዓት ቁምነገረኞችን የሚያስተናግድበት ቦታ የለውምና፡፡

የዋዘኝነት አንዱ ምንጭ ኃይማኖት ነው፡፡ ሃይማኖት ይህችን ምድር የሚያያት እንደጊዜያዊ መቆያ ነውና የሰው ልጅ ፍሬያማ ስራ ሰርቶ ለማለፍና የበለፀገች አገር ለልጁ ለማስተላለፍ ህልም አይኖረውም፡፡ ህልሙ ሰማይ ቤት ነው፡፡ ዓለምን የዋናው ህይወት መሸጋገሪያ ድልድይ አድርጎ የሚመለከት ህዝብ ድልድዩ ላይ እየተራመደ ስለሚሰራው ነገር ግድ የለውም፡፡ ከድልድዩ ማዶ እስኪደርስ ድረስ ጊዜ መግደያ ያስፈልገዋል…ቀልድ፡፡

የዋዘኝነት ሌላኛው ምንጭ ኋላቀርነት ነው፡፡ በቁስም ሆነ በሃሳብ ያልበለፀገ ህዝብ ዋነኛ መዝናኛው ወግ ነው፡፡ አምስት ሳንቲም የሌለው ሰው ከጓደኛው ጋር ሆኖ ሲዝናና ሊያመሽ ይችላል…ወግ እየጠረቀ፡፡ ሀበሻም ሌላ የሚዝናናበት ቁሳዊም ሆነ ሃሳባዊ ስልጣኔ ስለሌለው ወግ ሲያሳምርና ቧልት ሲያነጉት ይውላል፡፡ ማታ እሳት ዳር ተኮልኩሎ “እንካ ስለካንቲያ” ይላል፡፡ በስድብ ሲዝናና ያመሻል፡፡ የዋዘኛ ህዝብ ባህል ስድብ ነው፡፡ 

የአውሮጳ ጉብልስ? ምናልባት ስዕል ሲስል ወይም ኤሌክትሮኒክስ ሲፈታታ ወይም ድራማ ሲመለከት ወይም መፅሃፍ ሲያነብ ሊያመሽ ይችላል፡፡

በኤርሚያስ ለገሰ መፅሃፍ ውስጥ የተጠቀሱት የባለስልጣኖቻችን ቀልዶች ዋዘኝነት በዚያኛውም ወገን የተትረፈረፈ እንደሆነና ምን ያክል ደማችን ውስጥ እንዳለ የሚያሳይ ነው፡፡ እየተጫወተብንም ያለው እሱ ነው፡፡ ርሃብና ስደት እያላጋን እንዲህ ወግ ስናነብቅ ከዋልን ትንሽ ችጋራችን ቢላቀቅልን ምን እንሆን ነበር?

ቁምነገረኞች ሆይ የት ናችሁ?

No comments:

Post a Comment