Sunday, May 17, 2015

ስደትና ፖለቲካ




ስደትና ፖለቲካ


(ውብሸት ታደለ)

ኢትዮጵያውያን ካለቅጥ በመሰደድ ቀደሚውን ስፍራ የምንወስድ ህዝቦች መሆናችንን ዓለምም ሆነ እኛው ራሳችን የምናውቀው ነው፡፡ በየአገራቱ የሚቀበሉትን መከራና ስቃይ የሚሰማው ህዝብ፣ በየጊዜው የወንድሞቹንና የእህቶቹን ሰቆቃ አስመልክቶ እሪታ የሚያሰማው ህዝብ፣ ከስደት የተመለሰው ህዝብ፣ … አሁንም ስደትን ይመኛል፡፡ ከስደት በታች የሆነች አገር ይዘናል፡፡ ለዚህ አሳፋሪ አገራዊ ሁኔታ የመንግስታችን መልስ ሁሌም ተመሳሳይ ነው፡፡… “የግንዛቤ ችግር”፡፡ ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም ይህንን መልስ በየቦታው ሲደጋግሙት ይሰማሉ፡፡ ጉዳዩም ደላሎችን በማሳደድ ሊፈታ እንደሚችል ይናገራሉ፡፡ ይህ የቆዬ የመንግስት አቋም እንደሆነ አውቃለሁ፡፡ ጉዳዩን በዋናነት የሚከታተለው የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚንስቴርም ይህንኑ ሃሳብ ሲያራምድ አመታት ነጎዱ፡፡ 


አንድ ታሪክ ልንገራችሁ፡፡ ከአንድ የክልል ባለስልጣን ጋር የሆነ ቦታ እንገናኛለን፡፡ ስለግል ጉዳዮቼ ስናነሳ ቆይተን ውጭ አገር ስለመሄድ ተነሳ፡፡ ይህ ባለስልጣንም ምክሩን ለገሰኝ፡፡ “አገር ውሰጥ ሰርቶ መለወጥ ምናምን ሲባል የእውነት እንዳይመስልህ፤ በቻልከው አቅም ማምለጥ ነው” ሲል ወቀሰኝ፡፡ ይህ ባለስልጣን በሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ በኃላፊነት የሚሰራ ሲሆን በስደት ዙሪያ መግለጫ ሲሰጥ የሚውል ነው፡፡ ዶ/ር ቴወድሮስም በግል ቢያገኟችሁ እና የሚወዷችሁ ከሆነ ይህንን ምክር እንደሚደግሙላችሁ አትጠራጠሩ፡፡ 


ከሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ዓላማዎች ጥቂቶቹ ለዜጎች የስራ ስምሪት አገልግሎት መስጠት፣ የሰራተኞችን መብትና ደህንነት ማረጋገጥ ወዘተ ይገኙበታል፡፡ የሚገርመው ነገር ይህ ተቋም እንኳን ችግሩን ከስራ ስምሪት አንፃር ሊመለከተው አለመቻሉ ነው፡፡ ህዝብ በስራ እጦት፣ ባልተመጣጠነ ክፍያ፣ በለዬለት ድህነት አሳሩን እያዬ እነሱ “ግንዛቤ” የሚሉት ተረት ያወራሉ፡፡ የቻይና ካምፓኒዎች ውስኪ ይዘው ወደ ሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሲመላለሱ ማዬት ብርቅ አይደለም፡፡ ኃላፊዎችም የምስኪኑን ሠራተኛ ላብ በውስኪ ጠርሙስ ይጠጣሉ፡፡ እንዲህ እያዋረዱን ስለስደት ሊያስተምሩን ይፈልጋሉ፡፡ ባለስልጣኑ ስደት በሚመኝባት አገር ውስጥ ማነው ማንን ስለስደት የሚያስተምረው? 


አገራችን ከስደት ከፍታለች፡፡ 


በአንድ ወቅት ጌታቸው ረዳ የተባለው የኢህአዴግ ጡሩምባ ስለአንድ ኢህአዴግን ክዶ ውጭ ስለወጣ የኢህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣን ሲናገር ጉዳዩን ውጭ አገር ከመኖር ድሎት ጋር አገናኝቶት ነበር፡፡ ንግግሩን ስንተረጉመው አንድ የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣን ከስልጣኑ ይልቅ ውጭ አገር ሄዶ በጉልበቱ ሸቅሎ ማደር ይፈልጋል እንደማለት ነው፡፡ ምን ዓይነት የከፋ አገራዊ የኑሮ ሁኔታ ውስጥ ብንገኝ ነው ባለስልጣኖቻችን ሳይቀሩ ለኑሯቸው መሻሻል ስደትን ይመኛሉ እስከማለት ያደረሰን? የጌታቸው ንግግር በተዋረደ አገር ውስጥ የመኖራችንን ሃቅ ሳይፈልግ የሚመሰክር ነው፡፡ አገሪቱ ምን ያክል የጥቂቶች ብቻ እንደሆነችም የሚያሳይ ነው፡፡


ከአረብ አገራት የተመለሱ ዜጎች ከስደት እንደመጡ መንገድ ላይ ችፕስ መሸጥ፣ ገላን መሸጥ፣ ወዘተ. ጀምረው አልሳካ ሲላቸው ወደስደታቸው እንደተመለሱ አውቃለሁ፡፡ በግሌ ብዙ እንዲህ ያደረጉ ዜጎችን አውቃለሁ፡፡ እንግዲህ እነዚህ ሴቶች ይህን ችጋር መቋቋም ሲያቅታቸው መሰደዳቸው ነው የግንዛቤ ችግር ማለት፡፡ የጉድ አገር!


ሰሞኑን ደግሞ በስንት ጩኸት የተመለሱትን ስደተኞች ማዕከላዊ እንዳጎራቸው ሰማን፡፡ እነሱም አገር አለን ብለው መጥተው ለማዕከላዊ ሲዖል ተዳረጉ፡፡ የግንዛቤ ትምህርቱን ማዕከላዊ ሊሰጧቸው ይሆናል ፡) ፡( የጉድ አገር!!


እንደእውነቱ ከሆነ ለኢህአዴግ የሚሻለው የዜጎች መሰደድ ነው፡፡ ያ ባይሆን ኖሮ ዜጎች ለስደት የሚከፍሉትን መከራ ስርዓቱን ለመጣል ይከፍሉት ነበር፡፡ ወደ ሰሃራ ከማዝገም ወደ ደደቢት ይሮጡ ነበር፡፡ 


የዚያ ትውልድና የዚህ ትውልድ የጋራ ጉዳይ ጭቆና ነው፡፡ 


ያ ትውልድ በጭቆናው በመማረር ወደአገሪቱ ጫካዎች ተሰደደ፡፡ ይህ ትውልድ በጭቆናው በመማረር ከጫካዎቻችን ማዶ ተሰደደ፡፡ በዚያኛውም ሆነ በዚህኛው ትውልድ ስደቶች ውስጥ ሞትና ስቃይ አለ፡፡ የዚያ ትውልድ ስደተኞች ጫካ ውስጥ ሆነው ስለጭቆናቸው ያወራሉ፤ የዚህ ትውልድ ስደተኞች ከጫካው ማዶ ሆነው ስለጭቆናቸው ያወራሉ፡፡ ይህ ትውልድ ወደ ጫካው ቢሰደድ ኖሮ ኢህአዴግ አለቀለት ማለት አልነበረም?!


ስለዚህ ለኢህአዴግ የዜጎች ስደት ይሻለዋል፡፡


ጥቂቶችም በሰላም ውስኪያቸውን ይጠጣሉ፡፡


ግፍ ሲሰሩ ይውሉና ግፋቸውን በውስኪ ይረሳሉ፡፡ ህዝቡም ግፍ ሲቀበል ውሎ ግፉን በአረቄ ይረሳል፡፡ አረቄ የማይጠጡትም የስደትን ፅዋ ይጎነጫሉ፡፡ ክፋቱ ስደት ግፍን አያስረሳም፤ እንዲያውም ያስታውሳል እንጅ፡፡


ከመሰናበቴ በፊት ዶ/ር ቴወድሮስን አንድ ሙዚቃ ልጋብዛቸው፡


“Open your eyes and look within
Are you satisfied with the life you are living?
.
.
We know where we are from we know where we are going”
-Bob

No comments:

Post a Comment