Tuesday, May 26, 2015

ስትመርጥ የኖረች ሴት

ስትመርጥ የኖረች ሴት

(ውብሸት ታደለ)

ትረፍ ሲለኝ እንደ2002ቱ ምርጫ ሁሉ በዚህ መሳቂያ ምርጫም እጄን አላነካካሁም፡፡ ኢህአዴግ በቡጢ እንጅ በምርጫ እንደማይወድቅ ባውቅም የሰላማዊ ትግሉን የመጨረሻ ሙከራ ለመደገፍ አስቤ ካርድ ልወስድ ነበር፡፡ ሚካኤል በምህረቱ ዳሰሰኝና የውርደት ካርዱን ሳልቀበል ቀረሁ፡፡ ምናልባት ቀን ሲያልፍ ለልጄ በኩራት እነግረዋለሁ፤ “እኔ አባትህ ካርድ አልወሰድኩም ነበር” እያልኩ አወራዋለሁ፡፡

ያላደላቸው ወገኖቼ ካርዱን እንደዳረጎት እጅ ነስተው በመቀበላቸው በምርጫ ጣቢያው ተገኝተው ‘ይሆነኛል’ ያሉትን ጨጓራ በሽታን መርጠዋል፡፡ ከምርጫ ጣቢያው መልስም ወደ ጤና ጣቢያ እንዳዘገሙ ዘገባዎች ያመለክታሉ J

የመኢአድ ሊቀ-መንበር በክርክሩ ወቅት የተናገሩት ነገር አሁን ግልፅ እንደሆነላቸው መራጮቹ ለራሳቸው ተናግረዋል፡፡ ሊቀ-መንበሩ በክርክሩ ጊዜ ‘ህዝቡ በደም ግፊት ምናምን የሚጠቃው በሚደርስበት በደል እየተበሳጨ ነው’ ሲሉ ተናግረው ነበር፡፡ ዶ/ር ቴወድሮስ ይህን ነገር በጤና ፖሊሲው ውስጥ እንዲካተትና በምርጫ ቦርድና በኢቢሲ ምክንያት የሚከሰቱ በሽታዎችን እንዲቀንሱ አደራ እንላለን፡፡

ከዚሁ ጋር በተያያዘ ኢህአዴግ ለስኪዞፍሬንያ (የዕብደት በሽታ) መንስኤ ሆኖ ስለተገኘ አሳብዶ ሳይጨርሰን በፊት የአዕምሮ ጤናን በተመለከተ በኢህአዴግ ላይ ትኩረት ተደርጎ እንዲሰራ ለዶ/ር ቴወድሮስ አደራ እላለሁ፡፡ መቼም ዶ/ሩ “የውጭ ጉዳይ አይለምደኝም” ብለው ወደጤናው ይመለሳሉ ብዬ ነው አደራውን ለእርሳቸው መስጠቴ፡፡ እንደሌሎቹ ነባር ጓዶቻቸው ‘በእልህ መንቦራጨቄን እቀጥላለሁ’ ካሉም መንገዱን ጨርቅ ያድርግላቸው፡፡ ያውም የአልመዳ ጨርቅ! J በነገራችን ላይ ኮሮጆውን ያመረተው አልመዳ ነው የተባለው እውነት ነው? እንዲያውም ኢህአዴግ ምርጫውን ያዘጋጀው ከምርጫው ሳይሆን ከኮረጆው የሚያገኘውን ትርፍ አስቦ ነው ይባላል J

ድሮ ድሮ ኮረጆ ሲባል ቶሎ ወደአዕምሯችን የሚመጣው የቆሎ ተማሪ ነበር፡፡ ኮረጆ የምፅዋት መቀበያ ዕቃ ነበር፡፡ አሁን ግን ዕድሜ ለወያኔ ኮረጆ ሲባል ትዝ የሚለን ኢህአዴግ ነው፡፡ አሁን ኮረጆ የልመና ሳይሆን የዝርፊያ ዕቃ ነው፡፡ ከተመፅዋቾች ይልቅ ሌቦችን ያገለግላል፡፡

ድሮ ድሮ ካርድ ሲባል ትዝ የሚለን ጤና ጣቢያ ነበር፡፡ ካርድ የፈውስ ትኬት ነበር፡፡ አሁን ግን ዕድሜ ለገዢዎቻችን ካርድ ሲባል ትዝ የሚለን ምርጫ ጣቢያ  ነው፡፡ አሁን ካርድ የህመም ትኬት ነው፡፡ በውርደት ስሜት ምክንያት ለሚመጣ የጨጓራና የዕብደት በሽታ ያጋልጣል፡፡ ይህን በሽታ ለሃኪም ከተናገራችሁ ደግሞ ከጤና ጣቢያ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ትዛወራላችሁ፡፡

በነገራችን ላይ አንድ ለአምስት አደረጃጀት በህመምተኞች ላይ አልተሞከረም እንዴ? በመራጮች ላይ ተሞክሮ እኮ አመርቂ ውጤት አስገኝቷል፡፡ አንድ ሰው የአራት ሰው ድምፅ ይሰጣል፣ አንድ ሰው አራት ሰው ከምርጫ ጣቢያ ያባርራል፣ ወዘተ፡፡ እናንተዬ! እኔ የምፈራው ግን ወሲብ በአንድ ለአምስት ይሁን እንዳይሉን ነው ሃሃሃ አንድ ካድሬ ለአራት ሴቶች J

ጥርሴ ይርገፍ! አሁን ይሄ ከምርጫው በላይ የሚያስቅ ነገር ሆኖ ነው?!

…….

አንዲት ወዳጄ (ትደግዬ) በዚህ ወቅት አንድ የበዕውቀቱን ግጥም አስታውሳኛለች… “ስትፈጭ የኖረች ሴት”፡፡ በእርግጥም ስትፈጭ ኖራ በፈጨችበት ድንጋይ መቃብሯ የሚከደን ያች የገጠር እህታችን ስለዚህ ጉድ ምን ታውቃለች?!

እሷ የምታውቀው መፍጨት ነው፡፡ ገዢዎቿ ዱቄቷንም ድምጧንም ከከረጢቷ ይዘርፋሉ፡፡ ዱቄቷም ድምጧም የት እንደገቡ አይታወቅም፡፡ በሲሲፈስ ብርታት ሁሌም ዱቄት ትፈጫለች፤ ዱቄቱ ግን ቋቷን አይሞላም፡፡ በሲሲፈስ ብርታት ሁሌም ድምጧን ትሰጣለች፤ ድምጧ ግን ለገደል ማሚቶ እንኳን አይበቃም፡፡ … ስትመርጥ የኖረች ሴት!

“አታውቅም…
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ማን እንደሚባሉ
ሹማምንት በሷ ስም ምን እንደሚሰሩ
አነሳሁት እንጅ እኔም ለነገሩ
በፖለቲክ ጥበብ ራስን ማራቀቅ
ምን ይጠቅማትና ጓያዋን ለማድቀቅ”

(ካልረሳሁት እንዲህ እያለ ነው ግጥሙ የሚቀጥለው)

(በእንዲህ መልኩ ነው ኢህአዴግም የሚቀጥለው)

ሙሉውን ግጥም በማንበብ ሙሉውን የምርጫ ሂደት ይከታተሉ J … “ከቋት ስስት እንጅ ዱቄት አይታፈስ”!!

ግን በዘንድሮው ምርጫ ማን ያሸንፍ ይሆን?  J J 

ተስቶት ኢህአዴግ ካሸነፈ ግን ፕ/ር መርጋ ጠቅላይ ሚኒስትር ይሆናሉ… እየተባለ ነው ሃሃሃ
…….



Sunday, May 17, 2015

ስደትና ፖለቲካ




ስደትና ፖለቲካ


(ውብሸት ታደለ)

ኢትዮጵያውያን ካለቅጥ በመሰደድ ቀደሚውን ስፍራ የምንወስድ ህዝቦች መሆናችንን ዓለምም ሆነ እኛው ራሳችን የምናውቀው ነው፡፡ በየአገራቱ የሚቀበሉትን መከራና ስቃይ የሚሰማው ህዝብ፣ በየጊዜው የወንድሞቹንና የእህቶቹን ሰቆቃ አስመልክቶ እሪታ የሚያሰማው ህዝብ፣ ከስደት የተመለሰው ህዝብ፣ … አሁንም ስደትን ይመኛል፡፡ ከስደት በታች የሆነች አገር ይዘናል፡፡ ለዚህ አሳፋሪ አገራዊ ሁኔታ የመንግስታችን መልስ ሁሌም ተመሳሳይ ነው፡፡… “የግንዛቤ ችግር”፡፡ ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም ይህንን መልስ በየቦታው ሲደጋግሙት ይሰማሉ፡፡ ጉዳዩም ደላሎችን በማሳደድ ሊፈታ እንደሚችል ይናገራሉ፡፡ ይህ የቆዬ የመንግስት አቋም እንደሆነ አውቃለሁ፡፡ ጉዳዩን በዋናነት የሚከታተለው የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚንስቴርም ይህንኑ ሃሳብ ሲያራምድ አመታት ነጎዱ፡፡ 


አንድ ታሪክ ልንገራችሁ፡፡ ከአንድ የክልል ባለስልጣን ጋር የሆነ ቦታ እንገናኛለን፡፡ ስለግል ጉዳዮቼ ስናነሳ ቆይተን ውጭ አገር ስለመሄድ ተነሳ፡፡ ይህ ባለስልጣንም ምክሩን ለገሰኝ፡፡ “አገር ውሰጥ ሰርቶ መለወጥ ምናምን ሲባል የእውነት እንዳይመስልህ፤ በቻልከው አቅም ማምለጥ ነው” ሲል ወቀሰኝ፡፡ ይህ ባለስልጣን በሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ በኃላፊነት የሚሰራ ሲሆን በስደት ዙሪያ መግለጫ ሲሰጥ የሚውል ነው፡፡ ዶ/ር ቴወድሮስም በግል ቢያገኟችሁ እና የሚወዷችሁ ከሆነ ይህንን ምክር እንደሚደግሙላችሁ አትጠራጠሩ፡፡ 


ከሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ዓላማዎች ጥቂቶቹ ለዜጎች የስራ ስምሪት አገልግሎት መስጠት፣ የሰራተኞችን መብትና ደህንነት ማረጋገጥ ወዘተ ይገኙበታል፡፡ የሚገርመው ነገር ይህ ተቋም እንኳን ችግሩን ከስራ ስምሪት አንፃር ሊመለከተው አለመቻሉ ነው፡፡ ህዝብ በስራ እጦት፣ ባልተመጣጠነ ክፍያ፣ በለዬለት ድህነት አሳሩን እያዬ እነሱ “ግንዛቤ” የሚሉት ተረት ያወራሉ፡፡ የቻይና ካምፓኒዎች ውስኪ ይዘው ወደ ሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሲመላለሱ ማዬት ብርቅ አይደለም፡፡ ኃላፊዎችም የምስኪኑን ሠራተኛ ላብ በውስኪ ጠርሙስ ይጠጣሉ፡፡ እንዲህ እያዋረዱን ስለስደት ሊያስተምሩን ይፈልጋሉ፡፡ ባለስልጣኑ ስደት በሚመኝባት አገር ውስጥ ማነው ማንን ስለስደት የሚያስተምረው? 


አገራችን ከስደት ከፍታለች፡፡ 


በአንድ ወቅት ጌታቸው ረዳ የተባለው የኢህአዴግ ጡሩምባ ስለአንድ ኢህአዴግን ክዶ ውጭ ስለወጣ የኢህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣን ሲናገር ጉዳዩን ውጭ አገር ከመኖር ድሎት ጋር አገናኝቶት ነበር፡፡ ንግግሩን ስንተረጉመው አንድ የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣን ከስልጣኑ ይልቅ ውጭ አገር ሄዶ በጉልበቱ ሸቅሎ ማደር ይፈልጋል እንደማለት ነው፡፡ ምን ዓይነት የከፋ አገራዊ የኑሮ ሁኔታ ውስጥ ብንገኝ ነው ባለስልጣኖቻችን ሳይቀሩ ለኑሯቸው መሻሻል ስደትን ይመኛሉ እስከማለት ያደረሰን? የጌታቸው ንግግር በተዋረደ አገር ውስጥ የመኖራችንን ሃቅ ሳይፈልግ የሚመሰክር ነው፡፡ አገሪቱ ምን ያክል የጥቂቶች ብቻ እንደሆነችም የሚያሳይ ነው፡፡


ከአረብ አገራት የተመለሱ ዜጎች ከስደት እንደመጡ መንገድ ላይ ችፕስ መሸጥ፣ ገላን መሸጥ፣ ወዘተ. ጀምረው አልሳካ ሲላቸው ወደስደታቸው እንደተመለሱ አውቃለሁ፡፡ በግሌ ብዙ እንዲህ ያደረጉ ዜጎችን አውቃለሁ፡፡ እንግዲህ እነዚህ ሴቶች ይህን ችጋር መቋቋም ሲያቅታቸው መሰደዳቸው ነው የግንዛቤ ችግር ማለት፡፡ የጉድ አገር!


ሰሞኑን ደግሞ በስንት ጩኸት የተመለሱትን ስደተኞች ማዕከላዊ እንዳጎራቸው ሰማን፡፡ እነሱም አገር አለን ብለው መጥተው ለማዕከላዊ ሲዖል ተዳረጉ፡፡ የግንዛቤ ትምህርቱን ማዕከላዊ ሊሰጧቸው ይሆናል ፡) ፡( የጉድ አገር!!


እንደእውነቱ ከሆነ ለኢህአዴግ የሚሻለው የዜጎች መሰደድ ነው፡፡ ያ ባይሆን ኖሮ ዜጎች ለስደት የሚከፍሉትን መከራ ስርዓቱን ለመጣል ይከፍሉት ነበር፡፡ ወደ ሰሃራ ከማዝገም ወደ ደደቢት ይሮጡ ነበር፡፡ 


የዚያ ትውልድና የዚህ ትውልድ የጋራ ጉዳይ ጭቆና ነው፡፡ 


ያ ትውልድ በጭቆናው በመማረር ወደአገሪቱ ጫካዎች ተሰደደ፡፡ ይህ ትውልድ በጭቆናው በመማረር ከጫካዎቻችን ማዶ ተሰደደ፡፡ በዚያኛውም ሆነ በዚህኛው ትውልድ ስደቶች ውስጥ ሞትና ስቃይ አለ፡፡ የዚያ ትውልድ ስደተኞች ጫካ ውስጥ ሆነው ስለጭቆናቸው ያወራሉ፤ የዚህ ትውልድ ስደተኞች ከጫካው ማዶ ሆነው ስለጭቆናቸው ያወራሉ፡፡ ይህ ትውልድ ወደ ጫካው ቢሰደድ ኖሮ ኢህአዴግ አለቀለት ማለት አልነበረም?!


ስለዚህ ለኢህአዴግ የዜጎች ስደት ይሻለዋል፡፡


ጥቂቶችም በሰላም ውስኪያቸውን ይጠጣሉ፡፡


ግፍ ሲሰሩ ይውሉና ግፋቸውን በውስኪ ይረሳሉ፡፡ ህዝቡም ግፍ ሲቀበል ውሎ ግፉን በአረቄ ይረሳል፡፡ አረቄ የማይጠጡትም የስደትን ፅዋ ይጎነጫሉ፡፡ ክፋቱ ስደት ግፍን አያስረሳም፤ እንዲያውም ያስታውሳል እንጅ፡፡


ከመሰናበቴ በፊት ዶ/ር ቴወድሮስን አንድ ሙዚቃ ልጋብዛቸው፡


“Open your eyes and look within
Are you satisfied with the life you are living?
.
.
We know where we are from we know where we are going”
-Bob

Wednesday, May 13, 2015

አቦይ ስብሃትን እንደሰማኋቸው



አቦይ ስብሃትን እንደሰማኋቸው



(ውብሸት ታደለ)


በአጋጣሚ በመንደራችን መብራት ስለመጣ ቴሌቪዥን የማዬት ዕድል አገኘሁ፡፡ የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ዶ/ር አዲሱ ገ/መድህንና ሌሎች ሰዎች የመሩት ስብሰባ እየተላለፈ ነበር፡፡ ፈገግ ካሰኙኝ ንግግሮች መካከል የኢህአዴግ ፓርቲን በመወከል የቀረቡት አቶ ዘሪሁን ተሾመ (ከተሳሳትኩ አርሙኝ ፡) ) ያቀረቡት የሆድ-አደር ዘይቤን የተከተለ ንግግር አንዱ ነው፡፡ ይህን ስብሰባ ለመናቅ የዚህ ሰውዬ መገኘት ራሱ በቂ ነው፡፡ የመድረኩ ፀሃፊ አቶ ገብሩ ደግሞ የምራቸውን በብሶት እየተናገሩ ነበር፡፡ የአቶ ገብሩን ጥያቄዎች ለመመለስ አፋቸውን የከፈቱ ብዙዎች ቢሆኑም ጥያቄያቸውን ለመረዳት አዕምሯቸውን የከፈቱ ግን አልነበሩም፡፡ የአቶ አየለ ጫሚሶ የመንፈስ ወንድም አቶ ትዕግስቱ አወል ደግሞ ሌላው ኢህአዴግን በመወከል ክርክር ያደረገ ሰው ነበር፡፡ የፓርላማ ወንበር እንደጫት ቤት ወንበር “አብሽር” በመባባል የሚገኝ መስሎት ኢህአዴግን “አብሽር” ሲል አምሽቷል፡፡ ጥርስ ሳይኖረው እንዲህ ሆድ ያዘዘበት ጥርስ ቢኖረው ምን ሊያደርገን ኖሯል?! ፡)

በዚህ ሁሉ ድራማ መጨረሻ አካባቢ አቦይ ስብሃት የተናገሩት ነገር ልቤን ነክቶኛል፡፡ አቦይ እንዳሉት ተለይቶ የተጨቆነ ብሔር የለም… ሁሉም ብሄር ነው የተጨቆነው… ለድንጋይ መወራወር የሚያበቃ ነገር የለም፡፡ አቦይን በተሳሳተ መንገድ ተረድቻቸው ካልሆነ በስተቀር ሁሉም ብሄር እየተጨቆነ መሆኑን ያምናሉ፡፡ ግን ጭቆናው ድንጋይ እስከመወራወር አያደርስም ባይ ናቸው፡፡ ምን ዓይነት ጭቆና ነው ድንጋይ እስከመወራወር የሚያደርሰው? 

አቦይ በንግግራቸው ውስጥ የህዝቡን ብሶትና ቁጣ የተረዱ ይመስላል፡፡ የአብዮት ስጋት አለባቸው፤ ፍርሃት ይነበብባቸዋል፡፡ ኢቢሲም በየቀኑ የሚያንፀባርቀው ይህንን ስጋትና ፍርሃት ነው፡፡ የፖለቲካ ችግሮቻችን ሁሉ መነሻም ስጋትና ፍርሃት ናቸው፡፡ በስጋትና ፍርሃት ላይ ተመስርተው የሚወሰዱ የዘፈቀደ እርምጃዎችና ግፎች ሌላ ስጋትና ፍርሃት ይፈጥራሉ፡፡ ይህ ሂደት ሲደጋገም እውነተኛው አስፈሪ ጊዜ ይመጣል፡፡

አጋጣሚ ሆኖ በመንግስት ተቋም ውስጥ ባለሙያ ሆኜ አገልግያለሁ፡፡ ቢያንስ የመንግስትን አሰራርና ፍላጎቶች ለማወቅ ዕድል ሰጥቶኛል፡፡ ጉዳዩ የማሻሻያ ጥያቄ አይደለም፡፡ አጠቃላይ የስርዓቱ/የእሽክርክሪቱ ችግር ነው፡፡ ስርዓቱ ሊጠገን ወይም ሊሻሻል የሚችል አይደለም፡፡ በጥቅምና በስርቆት መሰረት ላይ የቆመ ስርዓት ነው፡፡ ብዙ ቦታዎችን በተለያዬ ስም በማከማቸት ሂስ የወሰዱ አለቆች እዚያው ወንበር ላይ ተቀምጠው፣ ምንም የማያውቁ ሰራተኞቻቸውን በኪራይ ሰብሳቢነት ስም እያሸማቀቁ የሚገዙባት አገር ናት ኢትዮጵያ ማለት፡፡ 

አንዳንድ ጊዜ ዝርዝራቸው በጣም ብዙ የሆኑ ነገሮችን ጥቂት ለመዘርዘር እንኳን የምንቸገርበት ጊዜ አለ፡፡ የዝርዝሩ መብዛት የመዘርዘር ሙከራችንን አስቀድሞ ከንቱ ስለሚያደርግብን፡፡ የስርዓቱ ችግሮች እንዲህ ዓይነት ተስፋ አስቆራጭ ዝርዝሮች ውስጥ የሚመደቡ ናቸው፡፡ ምናልባት አቦይ ስብሃት የእውነት የችግሩ ብዛት አልታያቸው ብሎ ከሆነ ለዚህ ነገር ሁለት ምክንያቶች ጎልተው ይታዩኛል፡፡ አንደኛው፣ ከውስጥ የመሆን ችግር ነው፡፡ በአንድ ስርዓት ውስጥ የስርዓቱ አካል ስትሆን የስርዓቱን ችግሮች ለመረዳት ይከብድሃል፡፡ አንድ ሰው ሽንት ቤት ውስጥ የሚኖር  ቢሆን የሽንት ቤቱን ሽታ ሊረዳው አይችልም፤ ይልቁንም ሽንት ቤቱን ሊጠቀም የሚመጣ ሌላ ሰው አፍንጫውን ይዞ ይሮጣል፡፡ ሁለተኛው፣ ራስን የማታለል ችግር ነው፡፡ ራሳችን የሰራናቸው ውሸቶች መልሰው ራሳችንን እንዲያሳምኑን መፍቀድ ነው፡፡ ራስን ማታለል ወይም ራስን መዋሸት ማለት ለሌሎች ከመዋሸታችን በፊት በውሸቱ ራሳችንን ማሳመን ማለት ነው፡፡ የአቦይ ስብሃት ንግግር በነዚህ ሁለት ምክንያቶች የተነሳ ካልሆነ ግን አቦይ ስብሃት አውቀውና አቅደው በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ንፁህ ተንኮል እየሰሩ ነው ማለት ነው፡፡ ይህን ጥያቄ ለአቦይ ስብሃት በማቅረብ በኩል አቤል አባተ ትተባበረኛለህ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ድርጅታችሁ መጠየቅን አልፎ አልፎ እንኳን የሚፈቅድ ከሆነ፡፡

በመጨረሻም አንድ ነጥብ ላንሳ፡፡ አንዳንድ ካድሬዎች የስርዓቱ አብዛኛው ችግር በበታች ሹማምንት የመጣ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ ደርጎችም የሚሉት ይህንኑ ነበር፡፡ የደርግ የቀበሌ ካድሬዎች ህዝቡን የረሸኑት ስርዓቱ ስለፈቀደላቸው ነበር፤ የአሁኖቹ የቀበሌ ካድሬዎች ህዝብ የማይረሽኑት ስርዓቱ ስላልፈቀደላቸው ነው፡፡ የአሁኖቹ ፌዴራል ፖሊሶችና ልዩ ኃይሎች ሰው የሚፈጁት ስርዓቱ ስለፈቀደላቸው ነው፤ ህዝብን የሚበድሉና በሙስና የተጨማለቁ ሹማምንት አገሪቷን የሞሏት ስርዓቱ ስለፈቀደላቸው ነው፡፡ የደርግ ሹማምንት ይህንን ያክል በዘረፋ ተግባር ያልተሰማሩት ስርዓቱ ስላልፈቀደላቸው ነበር፡፡ ስለዚህ ችግሩ የስርዓቱ ነው፡፡ ካንሰሩ የተሰራጨው ከላይ ጀምሮ ነው፡፡

ሃበሻ ሆይ! 

ጫንቃህ የተፈጠረው ቋጠሮ ሳይሆን ግፍ ለመሸከም ነውና በርታ፡፡ ዓይኖችህ ለእምባ፣ ጆሮዎችህ ለሙሾ፣ አፍህ ለእሪታ ተፈጥሯልና መከራህን ቻለው፡፡ ቅኔ ነህና የቅኔነት መዘዙን ትቋቋመው ዘንድ ፅናቱን ይስጥህ፡፡ እምቢ ካልክ ግን ሸክሙን እናወርድ ዘንድ አብረን እንጩህ፡፡

 ከዘፈን ያመለጡ ሰሚ ጆሮዎች ካገኘን፡፡
  

Sunday, May 10, 2015

የግንቦት ወሬ (ክፍል ሶስት)



                   የግንቦት ወሬ (ክፍል ሶስት)
(ውብሸት ታደለ)

የደርግ ሰዎች ያን ትውልድ እስኪደክማቸው ድረስ ገርፈውትና ገድለውት ሲያበቁ ከስልጣን ወረዱ፡፡ ያንን ያደረጉት ለአገሪቱ ደህንነት እንደሆነ እያወሩ ነው፡፡ ደግነቱ የሚሰማቸው የለም፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲሰማቸው የሚያስገድዱበት ጊዜ አልፏልና፡፡

አሁን ደግሞ የወያኔ ሰዎች በተራቸው ሰው ሲገርፉና ሲገድሉ ይውላሉ፡፡ ይህን የሚያደርጉት ለአገሪቱ ደህንነት እንደሆነ ያወራሉ፡፡ ቀን እስኪያልፍ ድረስ እያስገደዱ ወሬያቸውን ይግቱናል፡፡
አገሪቱም ለደህንነቷ የልጆቿን ደም የምትጠባ ቆሌ ሆናለች፡፡ የኢትዮጵያ ጤና የሚጠበቀው የልጆቿን ደምና እምባ ስትጠጣ ሆኗል፡፡ አገሪቱ የምትከበረው ልጆቿን ስታዋርድ፣ የምትለብሰው ልጆቿን ስታራቁት፣ ዳግም የምትወለደው ዳግም ልጆቿን ስትቀብር ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህዳሴ የሚፀናው በልጆቿ የግርፋት ሰምበር ነው፡፡ እነበፍቃዱ፣ እነማህሌት፣ እነአቤል፣ እነአብርሃ፣ እነተመስገን…ሲገረፉ ካላዬች ኢትዮጵያ ደህንነት አይኖራትም፡፡ ለኢትዮጵያ ደህንነት ኢትዮጵያውያን መገረፍ፣ መሰደድ፣ መዋረድ፣ መገደል አለባቸው፡፡ ይህ የጌቶቻችን የደህንነት ፍልስፍና ነው፡፡
ደርጎቹ አገር የሚመስላቸው መሬት ብቻ ነው፡፡ ለመሬቱ ደህንነት ህዝቡን እንግደለው ብለው ህዝቡን ገደሉ፡፡

የአሁኖቹ ደርጎች ግን “አገር ማለት ሰው ነው” ብለው ዘመሩ፤ እናም መሬቱን ሸጡ፡፡ መሬታችንን ሽጠው አወዳይና በለጨ ቃሙበት፡፡ በቢራና በውስኪ ሰከሩበት፡፡ ስካር ባሰረው አንደበት “አገር ማለት ሰው ነው” እያሉ በውድቅት ሌሊት ሲዘምሩ ሰማን፡፡

የቢራው ስካር ሲያበቃ ደግሞ በደም መስከር አማራቸው፡፡ እናም ለአገር ሲሉ የህዝቡን ደም አፈሰሱ፡፡ ለኦሮሚያ ልማት ሲሉ ኦሮሞዎችን ገደሉ፡፡ ጋምቤላ ትለማ ዘንድ የጋምቤላ ልጆች ማቀቁ፡፡ ለኢትዮጵያ ልማት ሲሉ ኢትዮጵያውያንን አዋረዱ፡፡ 

እናም መሬቱንም ሰውንም ናቁ፡፡ አገር ማለት ምንድነው? አዲሱ መዝሙር ገና አልወጣም፡፡…

የወያኔ ሰዎች በብዙ መልኩ ዕድለኞች ናቸው፤ ዕድላቸውን አልተጠቀሙበትም እንጅ፡፡ ትዕቢት የት ላይ እንደሚጥል ከደርግ የመማር ዕድል ነበራቸው፤ አላቸውም፡፡ ከህዝባቸው ጋር በቀላሉ መገናኘትና መደማመጥ የሚችሉበት የቴክኖሎጂ ዘመን ላይ ነው የመጡት፡፡ ጭቆናን የሚታገስ ጫንቃ ያለው ህዝብ አላቸው፡፡ ይህን ዕድላቸውን ግን ሊጠቀሙበት አልፈቀዱም፡፡ ነገ እንዳይታዘንላቸው እየሆኑ ነው፡፡ ግፋቸው ግድቡን ሞልቶ እየፈሰሰ ነው፡፡ ግፍ የሚፈጥረው ኃይል ደግሞ በሜጋ ዋት የሚለካ አይደለም፡፡ ዕልቆ-ቢስ ነው፡፡

በየትኛውም ቋንቋ ቢገለፅ የማይደበዝዝ አንድ እውነት አለ፡፡ ነፃነትን ፍለጋ የወጡ ልቦች ሳያገኟት አይመለሱም፡፡ ወይ በጉዞ ላይ እንዳሉ ነፃ ይወጣሉ፤ ወይም ጉዞው ነፃ ያወጣቸዋል፡፡ ይህን ሃቅ ረስታችሁት ከሆነ የበርሃ ማስታዎሻችሁን አገላብጡት፡፡ አለበለዚያ ግን አገር እየገደላችሁ መዝሙር አትቀያይሩ፡፡ አገር ማለት አገር ነው፤ ኢትዮጵያ ነች፡፡ ኢትዮጵያን በብልቶቿ አትጥሯት፡፡ መሬት፣ ሰው፣ ታሪክ፣…ብልቶቿ እንጅ ሁነቶቿ አይደሉም፡፡

እባካችሁ ጭካኔው ይብቃችሁ፡፡ እምባ ማዬት ባያሳዝናችሁ እንኳን እንዴት አይሰለቻችሁም?!

ጊዜው እየመጣ ነው፡፡ ከግንቦት ደመና ጋር የሚያጉረመርመው ድምፃችን ሳይዘንብ በፊት ከራሳችሁ ጋር ተማከሩ፡፡ የልጆቿን ደም የምትጠባና ልጆቿን እንደፍየል ወጠጤ የምትቆጥር አገር አንፈልግም፡፡ ልጆቿን የምታዋርድ አገር አንፈልግም፡፡ 

ጅቦች ሆይ አገራችንን መልሱልን!!