Friday, January 27, 2012

አገሬ!


"…የግጦሽ ሳር ሲለመልም፤ ሲሰማሩ ሰደድ ሜዳ
አዝመራው ጣል ከንበል ሲል፤ ከብቱ ለሆራ ሲነዳ
ፈረስ ግልቢያ ስሸመጥጥ፤ ከወፎች ዜማ ስቀዳ
ልቤ በንፋስ ተንሳፎ፤ በዋሽንት ዋይታ ሲከዳ…
ያችን ነው ኢትዮጵያ የምላት
እመብርሃን ረሳሻት?"
__________________________________[ሎሬት ጸ.ገ.መ]
በአቡነ ጴጥሮስ ሰቆቃ ውስጥ ልጅነት ያተመው የትዝታ ዱካ ነፍስ ዘርቶ አቡኑን ሲያንሰቀስቃቸው እንሰማለን፡፡ አገር ማለት ምንድነው ለሚሉ የሎሬቱን ፍልስፍና በአቡኑ ትናጋ እንዲሰሙ እመክራለሁ፡፡ "ያችን ነው ኢትዮጵያ እምላት"፡፡ ሰው በልጅነቱ ይዞት ከሚወለደው ቡጫቂ ስጋ ይልቅ በህይወት ዘመኑ በምግብና በስራ የሚገነባው ይበልጣል፡፡ ይህ ራሳችን የገነባነውን ስጋ ራሳችን በቀላሉ ቆርጠን መጣል አንችልም፤ ህመሙ ስፍር የለሽ ነው፡፡ መንፈስም ከስጋ የተለዬ አይደለም፡፡ በሕይወት ውጣውረድ የተገነባ የአገር ፍቅርን ቆርጦ መጣል አይቻልም፡፡ ልምዱን ሌላ ቦታ ሌላ አገር ማዳበር ሊቻል ይችል ነበር፡፡ ግን አልሆነም፡፡ የልጅነት ስጋና መንፈስ የተገነቡት በዚች አገር ዳረንጎት ነው፡፡ ከአዳም ዕድሜ በኋላ የምናልፍበት የህይወት ቁልቁለት ሁሉ ለማንነት ብዙም እርባና የለውም፡፡ ሲግመንድ ፍሮይድ እንዳለው ልጅነት የማንነታችን መሰረት ነው፤ ካለዚህ መሰረት ማንነት ይሉት ጎጆ አይታሰብም፡፡
"…ያችን የልጅነት እናት
አዛኝቱ እንዴት ብለሽ ጥርሶችሽን ትነክሽባት?"

No comments:

Post a Comment