Sunday, October 11, 2015

ጨርቅና ባንዲራ



ጨርቅና ባንዲራ

ባንዲራንና ተያያዥ ጉዳዮችን በተመለከተ አስቀያሚ የማነኮር ስራ የጀመረው ሟቹ ጠቅላያችን ነው፡፡ አንደኛ ባንዲራን ወደጨርቅነት አወረደው፡፡ ቢያንስ ልብስና ጨርቅ እንኳን እንደሚለያዩ አያውቁም ነበር ማለት ነው፡፡ መጋረጃና ጨርቅ አይለያዩም እንዴ ጎበዝ? መቀነትና ጨርቅ አይለያዩም እንዴ ጓዶች? ታዲያ ጨርቁ ለተወሰነ ዓለማ ሲውል የጨርቅነት ትርጉሙን አውልቆ እንደሚጥል መረዳት እንዴት ያቅታል?

ባንዲራ ብዙ ነገር የያዘ ክቡር ነገር ነው፡፡ It’s sacred after all. ባንዲራን በእንዲህ መንገድ መግለፅ ታቦትን ከመሳደብ አይተናነስም፡፡ አገር፣ ታሪክ፣ እውነት፣…ባንዲራው ውስጥ አሉ፡፡
አሜሪካኖች የቀደዱት አንድ የፍልስፍና መንገድ አለ፡፡ “Symbolic Interactionism” ይባላል፡፡ መሰረቱ ከነቻርለስ ፒርስና ዊሊያም ጄምስ የPragmatism ፍልስፍና ነው፡፡ በአጭሩ ለመግለፅ ያክል እነዚህ ፈላስፎች እንደሚሉት እውነታ የሚገኘው በነገሮች ምንነት ላይ ሳይሆን ሰዎች ለነገሮቹ በሚሰጧቸው ትርጉም ላይ ነው፡፡ ለነገሮች በዕለት ከዕለት ህይወታችን ውስጥ የምንሰጠው ትርጉም እሱ ነው የነገሮች ዕውነት ማለት፡፡

ይህ ፍልስፍና በተለይም በማንነት ቀረፃ ሂደት ላይ በጣም ይሰራል፡፡ በተለይ ባንዲራና ተያያዥ የማንነት ምልክቶችን አንስተን ስናወራ እንደ ጋሽ መለስ ከጨርቅነቱ በላይ መመልከት ካልቻልን አስቸጋሪ ነው፡፡ ባንዲራ ማለት የአገር ምልክት ነው፡፡ መለስ ባንዲራን ሲሳደብ አገራችን ነው የተሳደበው፡፡

ባንዲራን ከጨርቅ በላይ የማይመለከቱ ሰዎች ባንዲራን እንደበጀት ለየክልሉ ቢያከፋፍሉ፣ በባንዲራው ላይ ያሻቸውን ንቅሳት ቢያስቀምጡ፣ የባንዲራን ክብርና የሚፈጥረውን ስሜት ባይረዱ ብዙም አይገርምም፡፡ ባንዲራዬን አይቼ በስሜት የማላለቅስ፣ የማልፎክር፣ የማልጨፍር፣ ወዘተ ከሆነ ባንዲራው ባንዲራ አይደለም፡፡

ቀለሙ ምንም ይሁን የእኔነት ስሜት የሚፈጥር፣ ዜጋው በታሪኩና በማንነቱ እንዲኮራና እንዲፋቀር የሚያደርግና የማነሳሳት ስሜት የሚፈጥር ካልሆነ ትርጉም የለውም፡፡ ከሁሉም በላይ ባንዲራ Inspirational Power ያስፈልገዋል፡፡

ታሪክን ክደህና ለክህደትህ ምልክት ነቅሰህለት ባንዲራ ልትፈጥር አትችልም፡፡ መለስ እውነቱን ነው፤ የእሱ ባንዲራ ጨርቅ ነው፡፡ ውስጤን አያነሳሳም፡፡ ባንዲራ የሚሰራው ከደምና ከታሪክ ነው፡፡
ብሄራዊ መግባባት ያልተፈጠረበትና ከህሊናችን ጋር በአንዳች ምትኃታዊ ኃይል ያልተሳሰረ ባንዲራ ባንዲራ አይደለም፡፡ ጉዳዩ ስዕልና ቀለም የመቀያዬር ጉዳይ አይደለም፡፡ የመለስ አንደኛው ውርስ የባንዲራን ልዩ ኃይልና ትርጉም ማናጋቱ ነው፡፡ ባንዲራን በኮሚቴ መስራቱ ነው፡፡ ባንዲራን በስዕል ምርጫና በምክንያታዊ ትንታኔ ሊገልፀው መሞከሩ ነው፡፡

የዮናታንም ሙከራ ያው ነው፡፡ መለስ በወጣትነቱ እንዲህ ያደርገው ነበር! ፡)  

No comments:

Post a Comment